ለሀገር አቀፍ የብቃት ምዘና የሚያበቃ ሞዴል ፈተና
ኮሌጁ ከ1,800 በላይ ለሚሆኑ ተመራቂ ሰልጣኞች ለሀገር አቀፍ የብቃት ምዘና የሚያበቃ ሞዴል ፈተና መስጠት ጀመረ!! ጀነራል ዊንጌት ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የ2018 ዓ.ም ተመራቂ ሰልጣኞችን ለሀገር አቀፍ የሙያ ብቃት ምዘና (CoC) ብቁ የሚያደርገውን ተቋማዊ የሞዴል ምዘና በዛሬው ዕለት በይፋ መስጠት ጀመረ። ፈተናው ሰልጣኞች ወደ ስራ ዓለም ከመቀላቀላቸው በፊት ክህሎታቸውን የሚፈትሹበት ወሳኝ ምዕራፍ መሆኑ ተገልጿል። በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ስራና ክህሎት ቢሮ የተዘጋጀው ይህ ምዘና በ11 ዲፓርትመንቶች እና በ25 የሙያ ዘርፎች ስልጠናቸውን ላጠናቀቁ 1,876 ዕጩ ምሩቃን እየተሰጠ የሚገኝ ሲሆን በዚህ ምዘና 691 ወንድ እና 1,185 ሴት ተመራቂ ሰልጣኞች ይሳተፋሉ። ተመራቂዎቹ ከሚመዘኑበት አጠቃላይ ውጤት ውስጥ 30% የፅንሰ ሀሳብ (Theory) ምዘና በበይነ-መረብ (Online) እየተሰጠ ሲሆን 70%ቱ ደግሞ የተግባር (Practical) ምዘና በስልጠና ወርክሾፓቸው እየተመዘኑ ነው።.
Event Highlights
"የዚህ ተቋማዊ ሞዴል ዋነኛ ግብ ተመራቂዎቻችን ለሀገር አቀፉ የብቃት ምዘና ማዕከል ከመቅረባቸው በፊት ያላቸውን እውቀትና ክህሎት ለመፈተሽ እና ክፍተቶቻቸውን ለይቶ ለማረም ነው" ያሉት በኮሌጁ የስልጠና እና አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ዲን የሆኑት አቶ ጄበሳ ሙላቱ ናቸው። ምክትል ዲኑ አክለውም ሰልጣኞች በስራ ገበያው ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ብቃታቸውን ከፍ ለማድረግ በሚረዱ አምስት የተለያዩ ዘርፎች የልል ክህሎት (Soft Skills) ስልጠናዎች ከምዘናው ጎን ለጎን እየተሰጣቸው መሆኑን አብራርተዋል። በዛሬው ዕለት የኤሌክትሪካል ኤሌክትሮኒክስ፣ የሆቴልና ሆስፒታሊቲ፣ የሰርቬይንግና ድራፍቲንግ፣ የውድ ወርክ እንዲሁም የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ (ICT) ሞዴል ምዘናዎች የተሰጡ ሲሆን ቀሪዎቹ በ5 ቀናት ውስጥ ተጠናቀው ሁሉም ተመራቂዎች ለዋናው ፈተና ዝግጁ እንደሚሆኑ ታውቋል። በተያያዘ ዜና ሁሉም የበጀት ዓመቱ ተመራቂዎች የኮሌጁን የውስጥ ብቃት ምዘና ማለፋቸውም ተጠቁሟል።
Event Details:
Date & Time
july 15, 2026
10:00 AM - 2:00 PM
Venue
Main ICT Shop
General Wingate Polytechnic College